April 28, 2026

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

የማይክል ጃክሰን የሕይወት ታሪክ ፊልም የዓለምን የቦክስ ኦፊስ ክብረ ወሰን ሰበረ

በማይክል ጃክሰን የሙዚቃ ሕይወት ላይ ትኩረቱን አድርጎ የተሰራው አዲሱ ሙዚቃዊ ይዘት ያለው ፊልም በዓለም አቀፍ ደረጃ በቦክስ ኦፊስ ከፍተኛ ስኬት በማስመዝገብ በህይወት ታሪክ ፊልም ዘርፍ ከፍተኛውን የመጀመሪያ ሳምንት ገቢ አስመዝግቧል።

ፊልሙ ከዚህ ቀደም በአውሮፓውያኑ 2018 ተመርቆ በሳምንቱ መጨረሻ 124 ሚሊዮን ዶላር በማግኘት የቦክስ ኦፊስ ክብረ ወሰኑን ይዞ የነበረውን የኩዊን “ቦሂሚያን ራፕሶዲ” እና የ2024ቱን “ኦፐንሃይመር” በመብለጥ የዓለማችን ቁጥር አንድ የሕይወት ታሪክ ፊልም ሆኗል።

በማይክል ጃክሰን የወንድም ልጅ ጃፋር ጃክሰን ዋና ተዋናይነት የተሰራው ይህ ፊልም ባለፈው ረቡዕ ከተመረቀበት እለት ጀምሮ በዓለም አቀፍ ደረጃ በቦክስ ኦፊስ 217 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማስገባት ችሏል።

ምንም እንኳን ይህ ፊልም በፊልም ሃያሲዎች ዘንድ ዝቅተኛ ውጤት ቢሰጠውም፣ ከተመልካቾች ግን የ97 በመቶ ድጋፍ በማግኘት አድናቆትን አትርፏል።

እውቁ “የፖፕ ሙዚቃ ንጉሥ” በመባል በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚታወቀው ማይክል ጃክሰን የዜማ ደራሲና ዳንሰኛ ሲሆን በሙዚቃው ብቻ ሳይሆን ሙን ዎክ (Moonwalk) በተሰኘው የዳንስ ስልቱ እና በሙዚቃ ቪዲዮ አቀራረቡ የዘርፉን ኢንዱስትሪ የቀየረ ነበር።

ምንም እንኳን በህይወት ዘመኑ በተለያዩ አወዛጋቢ ጉዳዮች ውስጥ ቢያልፍም፣ በሙዚቃው ዓለም ላይ ያሳረፈው አሻራ ግን እስከ ዛሬ ድረስ የማይረሳ ነው። ማይክል ጃክሰን በተወለደ በ50 ዓመቱ ከዚህ ዓለም በሞት መለየቱ ይታወሳል።