የኢራን አብዮታዊ ዘብ ባለፉት 24 ሰዓት ውስጥ 25 የንግድ መርከቦች በሆርሙዝ ሰርጥ አልፈዋል አለ፡፡
የአብዮታዊ ዘቡ የባህር ኃይል እንዳስታወቀው÷ ኢራን ያስቀመጠችውን የቁጥጥር እና የደህንነት መስፈርቶችን በማሟላት በሆርሙዝ ሰርጥ የንግድ መርከቦች እየተላለፉ ነው፡፡
የነዳጅ እና እቃ ጫኝ መርከቦችን ጨምሮ በአጠቃላይ 25 የንግድ መርከቦች በአንድ ቀን ውስጥ በሆርሙዝ ሰርጥ መተላለፋቸውን ጠቅሶ፤ ኢራን በሰርጡ የምታደርገው ቁጥጥር መቀጠሉን ገልጿል።
እስራኤል እና አሜሪካ ጥቃት መፈጸማቸውን ተከትሎ ኢራን በፈረንጆቹ 2026 የካቲት ወር የሆርሙዝ ሰርጥን ሙሉ በሙሉ መዝጋቷ ይታወሳል፡፡
እንደ ፕሬስ ቲቪ ዘገባ፤ የኢራን አብዮታዊ ዘብ በሆርሙዝ ሰርጥ እያደረገ ባለው ቁጥጥር የሩሲያ እና ቻይና መርከቦች ቅድሚያ ተሰጥቷቸዋል።
ይህ የሆነው ሀገራቱ የኢራን አጋሮች በመሆናቸው የተገለጸ ሲሆን፤ በተቃራኒው የኢራን ወዳጅ ባልሆኑ ሀገራት መርከቦች ላይ ቀረጥን ጨምሮ ሌሎች ፍተሻዎች እየተደረገባቸው ነው።
በተለይም አብዮታዊ ዘቡ የኢራን ጠላቶች እና አጋሮቻቸው የሆኑ ሀገራት መርከቦችን የባለቤታቸውን እና የግንኙነት መስመራቸውን የመርመር እና የመርከቦችን የጭነት ይዘት በተመለከተ አካላዊ ፍተሻን ያደርጋል ነው የተባለው፡፡
ኢራን ያስቀመጠችውን ቁጥጥር ተከትሎ ዓለም አቀፍ የመርከብ ኩባንያዎች በሆርሙዝ ሰርጥ ላይ ያለውን ደህንነት ለማረጋገጥ ከኢራን ጋር በግል እየመከሩ ይገኛሉ።
More Stories
አሜሪካ ለዩክሬን የ108 ነጥብ 1 ሚሊየን ዶላር ወታደራዊ መሳሪያ ሽያጭ ልትፈጽም ነው
ኢራን የቻይናው ፕሬዚዳንት ያቀረቡትን ባለ አራት ነጥብ የሰላም የውሳኔ ሐሳብ እንደምትደግፍ ገለጸች