ማሻ፣ ጥር 01/2018 ዓ/ም (ማሻ ኤፍኤም 103.8) በ2018 ዓ.ም ለሚካሄደው 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የመራጮችና ዕጩዎች ምዝገባ ሂደት ስኬታማ እንዲሆንና ሊያጋጥሙ የሚችሉ ችግሮችን ለማስቀረት በርካታ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አስታውቋል።
ቦርዱ የምዝገባ ሂደቱን ዘመናዊና ምቹ ለማድረግ የቴክኖሎጂ ሥርዓት መዘርጋቱን ጠቁሞ ይህም መራጮችና ዕጩዎች ሊያጋጥማቸው የሚችለውን መጉላላትና ተፅዕኖ ለማስቀረት፣ አካል ጉዳተኞች (ዓይነ-ሥውራን) ራሳቸውን በራሳቸው እንዲመዘግቡ ለማስቻል እንዲሁም መራጮች ቋሚ መለያ ቁጥር እንዲኖራቸውና የመረጃ አያያዝን ሥርዓት ለማስያዝ ያለመ መሆኑን ቦርዱ ገልጿል።
በዚህም መራጮች “ምርጫዬ” የተባለውን የሞባይል መተግበሪያ በመጠቀም ራስን በራስ የመመዝገብ አማራጭ ተመቻችቶላቸዋል ብሏል።
በተጨማሪም በምርጫ ጣቢያዎች ታብሌቶችን በመጠቀም በምርጫ አስፈጻሚዎች አማካኝነት የሚከናወን የምዝገባ ሥርዓት የተዘረጋ ሲሆን፤ የቀደመውን አሠራር በመከተል በአካል በመገኘት በእጅ (በማንዋል) የመመዝገብ አማራጭም መጠቀም እንደሚቻል ተመልክቷል።
የምዝገባ ጊዜን በተመለከተ ቦርዱ ቀደም ሲል የራስን በራስ ምዝገባ ከጥር 15 እስከ መጋቢት 7 ቀን 2018 ዓ.ም. ለማከናወን አቅዶ የነበረ ቢሆንም፤ ሁሉም የምዝገባ አማራጮች ከፍትሐዊነት አንጻር በተመሳሳይ ጊዜ መጀመር ስላለባቸው ምዝገባው ከየካቲት 7 እስከ መጋቢት 7 ቀን 2018 ዓ.ም. እንዲከናወን ቦርዱ ተወስኗል።
በመሆኑም ቦርዱ የምዝገባ ምርጫ ጣቢያዎችን ዝርዝር በሕጉ መሠረት ከምዝገባው ቀን አስቀድሞ ይፋ እንደሚያደርግ አስታውቋል
More Stories
ዜጎች በመልዕክት መላላኪያ አማራጮች በሚፈጸሙ የሳይበር ጥቃቶች ተጋላጭ እንዳይሆኑ ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርባቸዋል፡-የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር
በሸካ ዞን አስተማማኝና ዘላቂ ሰላም ለማረጋገጥ እና የህግ የበላይነትን ለማስከበር ያለመ ዞናዊ የፀጥታ ግብረ ኃይል የምክክር መድረክ በቴፒ ከተማ ተካሄደ
ክልላዊ የተቀናጀ የማኅበረሰብ አቀፍ ተፋሰስ ልማት ማብሰሪያ ፕሮግራም በመካሄድ ላይ ይገኛል።