ማሻ፣ ታህሳስ 26/2018 ዓ/ም (ማሻ ኤፍኤም 103.8) ፤ አሜሪካ በቬንዙዌላ “ዘመቻ” በመክፈት ፕሬዝዳንት ኒኮላስ ማዱሮን በቁጥጥር ስር አዋለች። ባለፉት ቀናት ሲያወዛግብ የነበረው የአሜሪካና ቬንዙዌላ ጉዳይ ወደ “ወታደራዊ ዘመቻ” ያመራ ሲሆን፣ በአሜሪካ ቁጥጥር ስር የዋሉት ፕሬዝዳንት ማዱሮ እና ባለቤታቸው ወደ ኒዮርክ እየተወሰዱ መሆናቸው ተሰምቷል።
ፕሬዝዳንቱና ባለቤታቸው በአሜሪካ ለፍርድ ይቀርባሉ ያሉት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ እያካሄድን ነው ያሉትን ዘመቻ ከወራት በፊት በኢራን ከተፈጸመው ጥቃት ጋር አመሳስለውታል። አሜሪካ ባለፈው ዓመት ሰኔ ወር እስራኤልን ተከትላ በኢራን የኑክሌር መሰረተ ልማት ላይ የአየር ጥቃት መፈጸሟ ሲታወስ፤ የሀገሪቱ ጠቅላይ መሪ ላይ በእስራኤል ሊወሰድ ታቅዶ የነበረውን እርምጃ ውድቅ አድርጋ ነበር።
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አሜሪካ በቬንዙዌላ ያደረገችው “ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት” ዓለም አቀፍ ሕግን የሚሽር ነው ሲል መግለጫ አውጥቷል። የቬንዙዌላ ጎረቤት ኮሎምቢያ ደግሞ የስደተኞች ፍሰት ይጨምራል በሚል በድንበር አካባቢ ያለውን ጥበቃ ማጠናከሯ ተሰምቷል።
አሜሪካ ፕሬዝዳንት ማዱሮ በርካታ ‘የመብት ጥሰቶችን” የፈጸሙ መሪ ናቸው በማለት የምትከሳቸው ሲሆን፤ ሕጋዊ መሪ አይደሉም የሚል አቋም ስታንፀባርቅ መቆየቷን ቢቢሲ ዘግቧል።
More Stories
ዜጎች በመልዕክት መላላኪያ አማራጮች በሚፈጸሙ የሳይበር ጥቃቶች ተጋላጭ እንዳይሆኑ ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርባቸዋል፡-የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር
በሸካ ዞን አስተማማኝና ዘላቂ ሰላም ለማረጋገጥ እና የህግ የበላይነትን ለማስከበር ያለመ ዞናዊ የፀጥታ ግብረ ኃይል የምክክር መድረክ በቴፒ ከተማ ተካሄደ
ክልላዊ የተቀናጀ የማኅበረሰብ አቀፍ ተፋሰስ ልማት ማብሰሪያ ፕሮግራም በመካሄድ ላይ ይገኛል።