አሜሪካ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአለም አቀፉ ወንጀለኞች ፍርድ ቤት(አይሲሲ) ላይ ማዕቀብ እንዲጣል የሚጠይቀውን የውሳኔ ሀሳብ አጸደቀ፡፡
የውሳኔ ሀሳቡ በአለም አቀፉ ፍርድ ቤት ባላስልጣናት እና ተቋማዊ ንብረቶች ላይ ማዕቀብ የሚያሳልፍ ሲሆን በአሜሪካውያን እና በአጋሮቿ ላይ የእስር ማዘዣ እንዲወጣ የሚሰሩ አካላትን በቀጥታ ይመለከታል ተብሏል፡፡
መቀመጫውን በኔዘርላንድ ሄግ ያደረገው አለምአቀፋዊው ተቋም በተጠናቀቀው የፈረንጆቹ አመት በጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ እና በቀድሞ የመከላከያ ሚኒስትራቸው ዮአቭ ጋላንት ላይ ባወጣው የእስር ማዘዣ ነው ኮንግረሱ ማዕቀቡ እንዲጣልበት የወሰነው፡፡
በምክር ቤቱ የውጭ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ ተወካይ ብራየን ማስት የአለም አቀፍ የወንጀለኞች ፍርድ ቤትን “የካንጋሮ ፍርድ ቤት” ሲሉ ወርፈውታል፡፡
ለድምጽ የቀረበው የውሳኔ ሀሳብ በ243 ድጋፍ በ140 ተቃውሞ የጸደቀ ሲሆን በቀጣይ ሪፐብሊካኖች በርካታ ወንበር ወደ ያዙበት ሴኔት ተዘዋውሮ ድምጽ የሚሰጥበት ይሆናል፡፡
የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የመከላከያ ሚኒስትሩን ጨምሮ 3 ከፍተኛ የሀማስ ባላለስልጣናትን በጦር ወንጀል በመክሰስ ፍርድ ቤቱ የእስር ማዘዣ ያወጣው በህዳር ወር ነበር፡፡
በወቅቱ ኔታንያሁ “እስራኤል በአለም አቀፍ የወንጀለኛ ፍርድ ቤት የቀረበባት ክስ የማይረባ እና ከፖለቲካ ውግንና የተነሳ ነው” በሚል ውድቅ አድርገውታል።
አይሲሲ በሮም ስምምነት የተካተቱ አባላት ንቁ ተሳትፎ ሳያደርጉ ህጋዊ ውሳኔዎቹን የሚያስፈጽምበት ምንም አይነት መንገድ የለውም።
እስራኤል፣ ልክ እንደ አሜሪካ፣ ሩሲያ እና ቻይና ለፍርድ ቤቱ ስልጣን እውቅና አልሰጠችም፡፡
More Stories
ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ፡- በብዝኃነት ላይ የተመሠረተ ወል ትርክትን የመገንባት ጉዞ
የወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ ስራ ስኬታማነት ላይ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በቅንጅት ሊሰሩ ይገባል ተባለ
በብልፅግና ፓርቲ የሚመራው የመደመር መንግስት ያደሩ በርካታ የልማት ጥያቄዎችን ከመፍታት ባሻገር አዳዲሶቹን ጀምሮ በማጠናቀቅ የሕዝቡን ተጠቃሚነት እያረጋገጠ እንደሚገኝ አቶ ፍቅሬ አማን ገለጹ።