የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ ለቤንች ብሔር የዘመን መለወጫና የምስጋና በዓል “ቢስት ባር” የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።
ርዕሰ መስተዳድሩ የክልሉ ህዝቦች ቱባ የታሪክና የባህል እሴቶች ያሏቸው እንደ አንድ ቤተሰብ በባህላቸውና ትውፊታቸው የተሳሰሩ የውብና ማራኪ ባህሎች ባለቤቶች ናቸው ብለዋል።
በክልሉ ከሚገኙ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች መካከል አንዱ የቤንች ብሔር መሆኑን ያወሱት ርዕሰ መስተዳድሩ፤ በብሔረሰቡ ወግና ባህል መሠረት የራሱን የአዲስ ዓመት ማብሰሪያ ቀመር “ቢስት ባር” ከሌሎች ወገኖቹ ጋር አብሮ የሚያከብሩት ድንቅ እሴት ነው ሲሉም ተናግረዋል።
“ቢስት ባር” በቤንች ብሔር ዘንድ የአዲስ ዓመት ብስራት በመሆኑ ህዝቡ በአደባባይ በህብረት ሆነው ፈጣሪያቸውን የሚያመሰግኑበት ታላቅ በዓል ነው።
ይህ ድንቅ በዓል ለምቶ ጥቅም ላይ እንዲውል የክልሉ መንግስት የሚጠበቅበትን ሁሉ ያደርጋል ብለዋል በመልዕክታቸው።
የ”ቢስት ባር” ን ለሰላም፣ ለልማት፣ ለአብሮነትና ለወንድማማችነት እንዲሁም አብሮ ለመበልጸግ በሚያስችል መንገድ ጥቅም ላይ ማዋል ይገባልም ብለዋል።
በዓሉ የዞኑና የብሔሩ ብቻ ሳይሆን የክልሉም መገለጫ በመሆኑ የሀገርና የዓለም ጭምር እንዲሆን የክልሉ መንግስት ትኩረት ሰጥቶ ይሰራል ብለዋል በመልዕክታቸው።
በድጋሚ እንኳን ለቤንች ብሔር የዘመን መለወጫ “ቢስት ባር” በሰላም አደረሳችሁ ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ በዓሉ የሰላም፣ የፍቅር፣ የመተሳሰብና የአብሮነት እንዲሆን መመኘታቸውን ከክልሉ የመንግስት ኮሙኒኬሽን የተገኘ መረጃ ያመለክታል።
More Stories
ባለፉት ሦስት ዓመታት ለሰብዓዊ ድጋፍ በሚል የገባ ስንዴ የለም – አምባሳደር ሽፈራው ተክለማርያም (ዶ/ር)
በገጠሩ የሀገሪቱ አካባቢዎች መንግስት የሚዘረጋቸውን የተለያዩ ኢንሸቲቦችን ቀድሞና ፈጥኖ ተግባራዊ ከማድረግ አንፃር የተሻሉ አፈጻጸሞች መታየታቸው ተገለፀ ።
የሚኒስትሮች ምክር ቤት በ6 ጉዳዮች ላይ ውሳኔ አሳለፈ