July 11, 2026

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

በበጀት ዓመቱ የንግዱን ዘርፍ በቴክኖሎጂ በማገዝ ውጤታማ ተግባራት ተከናውነዋል – ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር)

በበጀት ዓመቱ የንግዱን ዘርፍ በማዘመንና በዲጂታል ቴክኖሎጂ በማገዝ ውጤታማ ተግባራት መከናወናቸውን የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ።

‎ሚኒስቴሩ ”የተደራጀ የዲጂታል አገልግሎት ለዘመናዊ የንግድ አገልግሎት” በሚል መሪ ሀሳብ የሴክተር ጉባኤውን በሀዋሳ ከተማ እያካሄደ ነው።

‎በመድረኩ መልዕክት ያስተላለፉት ሚኒስትሩ ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ በበጀት ዓመቱ የንግድ ዘርፉን ከማዘመን በተጨማሪ ዲጂታል አገልግሎትን በማጠናከር ውጤታማ ተግባራት ተከናውነዋል።

‎በተለይ የተገልጋዩን ጊዜና ጉልበት የሚቆጥቡ አገልግሎቶች ተደራሽ ለማድረግ የተደረጉ ጥረቶች ስኬታማ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ በዚህም ከ3 ነጥብ 4 ሚሊየን በላይ የንግድ ፈቃድና መሠል አገልግሎቶችን በኦን ላይን በመፈጸም የንግዱን ማህበረሰብ የአገልግሎት እርካታ 96 በመቶ ማድረስ ተችሏል ብለዋል።

‎የንግድ ፈቃድና የገበያ ቁጥጥርን በማጠናከር የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ያስቻሉ ውጤታማ ተግባራት መከናወናቸውንም አመልክተዋል።

‎በበጀት ዓመቱ 805 ተጨማሪ የቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎች መከፈታቸውን የገለጹት ሚኒስትሩ፤ በእዚህም በተመጣጣኝ ዋጋ ምርቶችን ለማህበረሰቡ በቀጥታ ማቅረብ በመቻሉ ገበያው እየተረጋጋ መምጣቱን አንስተዋል።

‎በበጀት ዓመቱ ወደ ውጭ ከተላኩ የተለያዩ ምርቶች ከ11 ቢሊየን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱንም አውስተዋል።

‎መንግስት የተከተለው የፖሊሲ አማራጭ ለዘርፉ ስኬታማነት ጉልህ ድርሻ ማበርከቱን ጠቁመው፤ በተለይ የብዝሃ ኢኮኖሚ ዘርፍ አቅጣጫ የኢኮኖሚ መሰረትን በማስፋት ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ መሆኑን ተናግረዋል።

‎የቁም እንስሳት ምርትን ወደ ውጭ በመላክ የሚገኘውን የውጭ ምንዛሬ ለማሳደግ ትኩረት እንደተሰጠና፣ ለእዚህም ከ10 በላይ የቁም እንስሳት የሽያጭ ማዕከላት መገንባታቸውን ጠቁመዋል።

‎በሀገሪቱ እየታየ ያለው ለውጥና እድገት የኢትዮጵያን በዓለም ደረጃ የመደራደር አቅም እንዲጨምር ማድረጉን ጠቅሰው፤ የተመዘገበውን ውጤት ይበልጥ አጠናክሮ ለማስቀጠል ዘመኑን የዋጀና በቴክኖሎጂ የታገዘ አገልግሎት ለማጠናከር ይሰራል ብለዋል።

‎በሴክተር ጉባኤው የሚኒስቴሩ ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ የሁሉም ክልሎች የዘርፉ የቢሮ ሀላፊዎች እና ባለድርሻዎች በመሳተፍ ላይ መሆናቸው ተመላክቷል፡፡