March 10, 2026

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

ማዕከሉ ስራ ከጀመረ ወዲህ 17 ሺህ 800 ዜጎች የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት አግኝተዋል_አቶ አስራት አዳሮ


‎‎ማሻ፤ መጋቢት 1/2018 ዓ/ም (ማሻ ኤፍ ኤም 103.8) የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ተደራሽነት በዞኖችና በከተማ አስተዳደሮች ለማስፋት ተግባራዊ እንቅስቃሴዎች መጀመራቸውም ተጠቁሟል።

‎የክልሉ መሶብ አንድ ማዕከል ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ አስራት አዳሮ እንደገለጹት በክልሉ ሚዛን-አማን ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ተመርቆ ለሕብረተሰቡ በሰፊው አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል።

‎በማዕከሉ አምስት የክልልና አራት የፌዴራል ተቋማት 35 የተለያዩ አገልግሎቶች እየተሰጡ የሚገኙ መሆናቸውን የገለጹት አቶ አስራት ማዕከሉ አገልግሎት መስጠት ከጀመረበት ጥቅምት ወር ወዲህ 17 ሺህ 800 ዜጎች አገልግሎት ማግኘታቸውን አስረድተዋል።

‎መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መጀመር በመንግስት አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ከሕብረተሰቡ ሲነሳ የነበረውን እንግልት እና ብልሹ አሰራሮችን በሰፊው እየቀረፈ እንደሚገኝ ዋና ስራ አስፈፃሚው ገልጸዋል።

‎አገልግሎቱ በተቀመጠ ስታንዳርድ መሠረት በዲጂታል የሚከናወን በመሆኑ አላስፈላጊ ምልልሶችን በመቅረፍ ጊዜ፤ የሚወጣ ሀብትና ጉልበት መቆጠብ እንዳስቻለም አቶ አስራት አብራርተዋል።

‎በትራንስፖርት፤ በፍትህ በሌሎች ዘርፎች ተጨማሪ አገልግሎት መሰጠት የሚያስችሉ ሶፍትዌሮች የማበልጸግ ስራ እየተከናወነ መሆኑ የተናገሩት ዋና ስራ አስፈፃሚው ዲጂታል ሲቪል ሰርቪስ ግንባታ በክልሉ ለማስፋት እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል።

‎የማዕከሉን አገልግሎት አሰጣጥ ተደራሽነት ለማስፋት በዞን ደረጃ የማዕከሉ ግንባታ ስራ የተጀመረ መሆኑን የገለፁት አቶ አስራት ግንባታው በሌሎች 15 ከተማ አስተዳደሮች የሚቀጥል መሆኑን ገልጸዋል።

‎በማዕከል አገልግሎት በማግኘት ላይ እያሉ ያነጋገርናቸው ባለጉዳዮች በበኩላቸው የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት የዜጎችን ጊዜ፤ ጉልበትና ወጪ መቆጠብ ያስቻለ ነው ብለዋል።

‎አገልግሎት አሰጣጡ በዲጂታል አሰራር የሚከናወን በመሆኑ ከፌዴራል እስከ ክልል ያሉ ጉዳዮቻቸውን በአንድ ጊዜ ለማስፈፀም ያስቻለ በመሆኑ ከአላስፈላጊ እንግልት መታደጋቸውን አስተያየት ሰጪዎቹ ተናግረዋል።

‎#SWMN