February 25, 2026

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

በክልሉ የህዝብ ለህዝብ ግኑኝነት እንዲጠናከር በማድረግ የብሔረሰቦች ፍትሃዊ የጋራ ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ ነው ፦ አቶ ጌታቸው ኬኒ የክልሉ ብሔረሰቦች ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ

ማሻ፤ የካቲት 17/2018 ዓ/ም (ማሻ ኤፍ ኤም 103.8) የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ብሔረሰቦች ምክር ቤት የ2018 ዓ.ም የ6 ወራት ዕቅድ አፈፃፀም የግምገማ መድረክ በሸካ ዞን ቴፒ ከተማ አካሂዷል ።

የክልሉ ብሔረሰቦች ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ አቶ ጌታቸው ኬኒ በወቅቱ እንደገለፁት ምክር ቤቱ  ግልፀኝነትና ተጠያቂነት በሰፈነበት አግባብ የብሔረሰቦች የጋራ ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል ።

በክልልሉ ውስጥ የሚገኙ ብሔረሰቦች ባህል ፣ታሪክ፣ ቋንቋ እና መልካም ዕሴቶች እንዲጎለብት ከማድረግ አንፃር ልዩ ትኩረት መሰጠቱን ያነሱት ዋና አፈ ጉባኤው ባለፍት ስድስት ወራት የተከናወኑ ጠንካራ ተግባራትን በማስቀጠል መስተካከል በሚገባቸው ጉዳዮች ላይ ትኩረት ይደረጋል ሲሉ ጠቁመዋል ።

በክልሉ የሚከሰቱ አለመግባባቶችን ሀገር በቀል የሆኑ እውቀቶችን በመጠቀም የመፍታት ባህል እንዲዳብር የማድረግ ስራዎች ላይ ምክር ቤቱ በስፋት እየሰራ  መሆኑን የገለፁት ደግሞ የክልሉ ብሔረሰቦች ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ አቶ መሰለ ከበደ ናቸው ።

በግምገማው መድረክ ላይ የክልሉ ብሔረሰቦች ምክር ቤት የ2018 ዓ.ም የ6 ወራት ዕቅድ አፈፃፀም ሪፓርት በቀረበበት ወቅት የብሔር ብሔረሰቦች የጋራ መግባባት እንዲፈጠር የሀገር ሽማግሌዎችንና የዘርፉ ባለሙያዎችን በማሳተፍ ሀገር በቀል የሆኑ እውቀቶችን የማጎልበት ስራ መሰራቱ ተጠቁሟል ።

የብሔረሰቦች ባህል ፣ታሪክ፣ ቋንቋ እና መልካም ዕሴቶች እንዲጠናከሩና ሀገር በቀል የሆኑ እውቀቶችን በመጠቀም የተጀመሩ መልካም ዕሴት ግንባታ ስራዎች ማስቀጠል እንደሚያስፈልግ የውይይቱ ተሳታፊዎች ጠቁመዋል ።