ማሻ ፣ የሰኔ 02፣ 2017 (ማሻ ኤፍ ኤም) ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ ለክልሎች የሚከፋፈለው የጋራ ገቢ የድጎማ በጀት እያደገ መምጣቱን የፌዴሬሽን ምክር ቤት አስታወቀ።
በውስን ዓላማ የድጎማ በጀቶች ትልልፍ እና በጋራ ገቢዎች ክፍፍል በሚስተዋሉ ተግዳሮቶች ላይ የዳሰሳ ጥናት የምክክር መድረክ እየተካሄደ ይገኛል።
የፌዴሬሽን ምክር ቤት ከሀገራዊ ለውጡ በኋላ የሀብት ክፍፍል ፍትሐዊነትን ለማረጋገጥ በርካታ ሥራዎች ማከናወኑን የምክር ቤቱ አፈ ጉብኤ አገኘሁ ተሻገር ገልጸዋል።
ከዚህ ውስጥ የጋራ ገቢዎች ማከፋፈያ ቀመር አንዱ ሲሆን በክልሎች የድርሻ ክፍፍል ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱንም ጠቁመዋል።
የክልሎች የጋራ ገቢ የድጎማ በጀት ክፍፍል ከለውጡ በፊት ከነበረበት 4 ቢሊዮን ብር ወደ 70 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር ማደጉን አፈ ጉባኤው ተናግረዋል።
ውስን ዓላማ የድጎማ በጀቶች ላይ የግልጸኝነት እና የተጠያቂነት ችግሮች ሲነሱ መቆየታቸውን አስታውሰዋል።
የዳሰሳ ጥናቱ ገቢ በሕግ አግባብ ወደ ክልሎች እና ከተማ አስተዳድሮች መተላለፉን እንዲሁም ፍትሐዊነት፣ ግልጽነት፣ አሳታፊነት እና ተጠያቂነት ያለው መሆኑን ለማረጋገጥ ይረዳል ብለዋል።
በተጨማሪም ክፍተት ያሉባቸው ጉዳዮችን በመለየት ለሚመለከታቸው አካላት ግብረመልስ በመስጠት እንዲታረሙ ለማድረግ እንደሚያስችል አቶ አገኘሁ ተሻገር ተናግረዋል።
በፌዴሬሽን ምክር ቤት የድጎማ በጀት እና የጋራ ገቢዎች ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ የቀረበው በውስን ዓላማ የድጎማ በጀቶች ትልልፍ ላይ የተደረገ የዳሰሳ ጥናት ሪፖርቱ የግልጽነት፣ የአሳታፊነት፣ የግንዛቤ እና የተጠያቂነት ችግሮች መኖራቸውን አመልክቷል።
የምክር ቤቱን የአሠራር ሥርዓት ተከትሎ ከመሥራት አንፃር ሰፊ ክፍተቶች መኖራቸውም ነው የተገለጸው።
በ2017 በጀት ዓመት ከ215 ቢሊዮን ብር በላይ ውስን ዓላማ ያላቸው የድጎማ በጀቶች ለክልሎች መተላለፋቸው ተመላክቷል።
ኢቢሲ
More Stories
በቀጣይ 90 ቀናት የተቀመጡ ዕቅዶችን በውጤታማነት በመፈጸም እመርታዊ ውጤት ለማስመዝገብ ርብርብ ማድረግ ይኖርብናል፦አቶ ፍቅሬ አማን
ምክር ቤቶች የህዝቡ ሁለተናዊ ተጠቃሚነት እንድረጋጥ ድርሻቸው የጎላ በመሆኑ የድጋፍና ክትትል ስራዎችን ማጠናከር እንደምያስፈልግ ተጠቆመ ።
ኢትዮጵያ ስደተኞችን ተቀብላ በማስተናገድ እያከናወነች ያለው ተግባር የሚደነቅ ነው