ከ4 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት ንብረቶችን ሰርቀዋል በሚል የተጠረጠሩ ግለሰቦች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታወቀ። መስከረም 3 ቀን 2017 ዓ.ም ከሌሊቱ 10 ተኩል በቂርቆስ ክፍለ ከተማ በወረዳ 5 በመገንባት ላይ በሚገኘው አዳምስ ህንፃ ላይ የተዘረጉ የኤሌትሪክ ገመዶችን ለመስረቅ ሁለት ተጠርጣሪዎች አጥር ዘለው ሲገቡ በወቅቱ በወንጀል መከላከል ስራ ላይ በነበሩ የፖሊስ አባላት ተይዘው ሲፈተሹ የኬብል መቁረጫና ሁለት ቦርሳ እንደተገኘባቸው ፖሊስ ጠቅሷል። የተፈፀመውን ወንጀል መነሻ በማድረግ በተጠርጣሪዎች ላይ ምርመራ ማስፋት ስራ መስራቱን የቂርቆስ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ ገልጿል። በምርመራ ማስፋት ሥራው ግለሰቦቹ በክፍለ ከተማው ወረዳ 1 በፀጋ ሆስፒታል አካባቢ ከሚገኘው አንድ ግለሰብ መኖሪያ ቤት የሰረቁትን ንብረት እንደሚያስረክቡ በመረጋገጡ በህግ አግባብ በተደረገ ብርበራ 50 ጥቅል የኤሌትሪክ ገመዶች፣ 5 ጥቅል የኤል ኢ ዲ ኬብል፣ ልዩ ልዩ አይነት ሌሎች ኬብሎች እና ልዩ ልዩ ቁሳቁሶችን እንዲሁም ከዚህ ቀደም ከአዳምስ ህንፃ የተሰረቁ የኤሌትሪክ ገመዶች መገኘቱን ፖሊስ መምሪያው አስታውቋል። ከዚህ የወንጀል ድርጊት ጋር በተገናኘ የስርቆት ወንጀል በመፈፀም የተጠረጠሩና የተሰረቀ እቃ የሚገዙ ሁለት ተቀባዮች ተይዘው ምርመራው ተጠናክሮ መቀጠሉን ፖሊስ ጨምሮ ገልጿል።
EBC
More Stories
ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ፡- በብዝኃነት ላይ የተመሠረተ ወል ትርክትን የመገንባት ጉዞ
የወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ ስራ ስኬታማነት ላይ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በቅንጅት ሊሰሩ ይገባል ተባለ
በብልፅግና ፓርቲ የሚመራው የመደመር መንግስት ያደሩ በርካታ የልማት ጥያቄዎችን ከመፍታት ባሻገር አዳዲሶቹን ጀምሮ በማጠናቀቅ የሕዝቡን ተጠቃሚነት እያረጋገጠ እንደሚገኝ አቶ ፍቅሬ አማን ገለጹ።