April 23, 2026

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

ቻይና ለመጀመሪያ ጊዜ የጠፈር ጣቢያዋን ለውጭ ሀገር ጠፈርተኞች ክፍት አደረገች

ቻይና በጠፈር ምርምር ታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ የውጭ ሀገር ዜግነት ያላቸውን ጠፈርተኞች ወደ “ቲያንጎንግ” የጠፈር ጣቢያዋ ልትልክ መሆኑን አስታውቃለች።

“ቲያንጎንግ” ወይም “የሰማይ ቤተመንግስት” ተብሎ የሚጠራው ይህ ግዙፍ የሳይንስ ላብራቶሪ፣ እስካሁን ለቻይናውያን ጠፈርተኞች ብቻ ሲያገለግል የቆየ ቢሆንም፣ አሁን ግን የፓኪስታን ተወላጅ ለሆኑት ሙሐመድ ዚሻን አሊ እና ኩራም ዳውድ በሩን ክፍት አድርጓል።

እነዚህ ሁለት ጠፈርተኞች በቅርቡ ወደ ቻይና በመጓዝ በጠፈር ጣቢያው ውስጥ ለሚኖራቸው ቆይታ የሚያግዛቸውንና ከባድ የተባለውን የተግባር ስልጠና ይጀምራሉ።

ይህ ታሪካዊ ውሳኔ ቻይና በጠፈር ምርምር መስክ ያላትን የቴክኖሎጂ ልዕልና ለሌሎች ሀገራትም ለማጋራትና የዓለም አቀፍ ትብብርን ለማጠናከር ያላትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው።

በተለይም እንደ ፓኪስታን በዘርፉ ላይ በትጋት እየሰሩ ላሉ ሀገራት፣ ይህ ጉዞ እጅግ ዘመናዊ ከሆነው የቻይና የጠፈር ቴክኖሎጂ ጋር በቀጥታ እንዲተዋወቁና ትልቅ ልምድ እንዲቀስሙ ሰፊ እድል ይከፍትላቸዋል።

እንደ ሲጂቲኤን ዘገባ ከሆነ፣ ይህ እርምጃ ከሳይንሳዊ ትብብር ባለፈ በቻይና እና በፓኪስታን መካከል ያለውን ስትራቴጂካዊ ግንኙነት ወደ ላቀ የቴክኖሎጂ እና የሳይንስ ከፍታ የሚያሸጋግር ነው።

ቻይና የጠፈር ጣቢያዋን ለሌሎች ሀገራት ክፍት ማድረጓ ወደፊት በርካታ ሀገራት በጋራ የሚሰሩበት ዓለም አቀፋዊ የጠፈር ምርምር ማዕከል የመሆን ተስፋውን ይበልጥ እንዲያብብ አድርጎታል።