March 23, 2026

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

የትራምፕ የ48 ሰዓት የጊዜ ገደብ እና የኢራን ምላሽ

የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ዛቻና ማስፈራሪያ የኢራንን አንድነት የበለጠ ከማጠናከር ውጭ የሚያመጣው ለውጥ አይኖርም አሉ የኢራኑ ፕሬዚዳንት መሱድ ፔዜሽኪያን፡፡

ዶናልድ ትራምፕ ኢራን የሆርሙዝ ሰርጥን ካልከፈተች አሜሪካ በቴህራን የኢነርጂ መሰረተ ልማቶች ላይ ጥቃት እንደምትፈጽም የሰጡት የ48 ሰዓታት የጊዜ ገደብ ዛሬ ምሽት ይጠናቀቃል፡፡

የኢራን ፕሬዚዳንት መሱድ ፔዜሽኪያን ለፕሬዚዳንት ትራምፕ ማስጠንቀቂያ በሰጡት ምላሽ፥ ኢራንን የማዳከምና ከዓለም ካርታ ላይ የማጥፋት ሙከራ በኢራን የቁርጥ ቀን ልጆች እየከሸፈ ይገኛል ብለዋል፡፡

የዶናልድ ትራምፕ ዛቻና ማስፈራሪያዎች የኢራንን አንድነት የበለጠ ያጠናክሩታል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፥ መሰል የሽብር ዛቻዎችን በጦር ሜዳ እንጋፈጣቸዋለን ነው ያሉት፡፡

ግዛታችንን ከተዳፈሩት ጠላቶች በስተቀር የሆርሙዝ ሰርጥ ለሁሉም ሀገራት ክፍት ነው ሲሉም ነው ፕሬዚዳንቱ ያስታወቁት፡፡

በሌላ በኩል ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር ኬር ስታርመር ጋር የሆርሙዝ ሰርጥን ለማስከፈት ያለመ ምክክር ማድረጋቸው ተሰምቷል፡፡

የእስራኤል ወታደራዊ ሀይል በበኩሉ ከኢራን እና ሂዝቦላህ ጋር እያደረገ ያለው ጦርነት በርካታ ሳምንታትን እንደሚፈጅበት አስታውቋል፡፡

አራተኛ ሳምንቱን ሊይዝ በተቃረበው ጦርነት ኢራን እና እስራኤል ጥቃት እየተሰነዛዘሩ ሲሆን፥ እስራኤል በሊባኖስ እያደረገች ባለው የእግረኛ ጦር ዘመቻ ከ1 ሺህ በላይ ሰዎች ተገድለዋል መባሉን አልጀዚራ ዘግቧል፡፡