February 4, 2026

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

ኪነ-ጥበብና ባህል ብዝሃነታችንን የሚያስተሳስሩ የኢትዮጵያዊነት ማገር ናቸው – ወ/ሮ ሸዊት ሻንካ

ማሻ፣ ጥር 07/2018 ዓ/ም (ማሻ ኤፍኤም 103.8) ኢትዮጵያዊ የኪነ-ጥበብና የባህል እሴቶች ብዝሃነታችንን የሚያስተሳስሩ የኢትዮጵያዊነት ማገር ናቸው ሲሉ የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ወ/ሮ ሸዊት ሻንካ ገለጹ።

ሚኒስትሯ በታሪካዊቷ የጎንደር ከተማ እየተካሄደ በሚገኘው ኪን-ኢትዮጵያ መድረክ ላይ በመገኘት የመክፈቻ ንግግር አድርገዋል።

በንግግራቸው፤ ኢትዮጵያ የበርካታ ብሔር ብሔረሰቦች እና ቋንቋዎች ባለቤት መሆኗን ጠቅሰው፣ ይህ ብዝሃነት ውበታችንና መገለጫችን መሆኑን ገልጸዋል።

ጥበባትና ባህል ደግሞ ሕዝቡን በጋራ እሴቶች በማስተሳሰር፣ አብሮነትን እና ማህበራዊ ትስስርን ለማጠናከር እጅግ ግዙፍ አቅም እንዳላቸው አስገንዝበዋል።

ወይዘሮ ሸዊት አክለውም፣ የመደመር መንግስት ለኪነ-ጥበብና ለባህል እሴቶች ከየትኛውም ጊዜ በላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል ብለዋል።

በተለይም ጥበባት እንዲጠኑ፣ እንዲለሙና ለቀጣዩ ትውልድ ሳይበረዙ እንዲተላለፉ የተለያዩ ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን አብራርተዋል።

የኢትዮጵያን ቱባ ባህልና ታሪክ የሚያሳዩ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ሁነቶችን በማዘጋጀት የሀገራችንን ገጽታ የመገንባት ሥራ በስፋት እየተሰራ መሆኑንም አንስተዋል።

ሚኒስትሯ በንግግራቸው ማጠቃለያ፣ ለትውልዱ ባህሏ የዳበረ ሀገርን ለማቆየት የሁሉም ዜጋ የጋራ ጥረት እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል። ለልጆቻችን ቀጣይ ሕይወት ምቹ ምህዳርን ለመፍጠር በጋራ መሥራት ይጠበቅብናል ሲሉም ጥሪ አቅርበዋል።

በመጨረሻም በጎንደር ከተማ ቆይታቸው ለተደረገላቸው ደማቅና ኢትዮጵያዊ ለዛ ላለው የእንግዳ አቀባበል ምስጋና አቅርበዋል።

#EBC