December 25, 2025

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

ሀብትን በተገቢው ማሳወቅና ማስመዝገብ ሙስናና ብልሹ አሰራሮችን በመከላከል ግልፀኝነት እንዲፈጠር ፋይዳው የጎላ በመሆኑ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ተገለፀ ።

ማሻ፣ ታህሳስ 15/2018 (ማሻ ኤፍ ኤም 103.8) የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል መንግሥት የስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ትውልድን በስነ – ምግባር ተቋምን በአሰራር” በሚል መሪ  አዲስ ለተመደቡና እና ለነባር የስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ዳይሬክተሮች ፣ቡድን መሪዎችና ባለሙያዎች የአሰልጣኞች ስልጠና በሚዛን ቴፒ ዩንቨርስቲ ቴፒ ግቢ በመስጠት ላይ ይገኛል ።

ሙስናና ብልሹ አሰራሮች የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን በማደናቀፍ በህዝብ እና በመንግሥት መካከል ያለውን ግኑኝነት በማሻከር በሀገር ዕድገት ላይ አሉታዊ ተጽዕኖዎችን የሚያስከትሉ መሆናቸው ይታወቃል።

የክልሉ ስነ-ምግባር እና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙሉሰው ዘውዴ በወቅቱ እንደገለፁት ሀብትን በተገቢው ማሳወቅና ማስመዝገብ ሙስናና ብልሹ አሰራሮችን ከመከላከል ባሻገር ግልፀኝነትን እንዲፈጠር ያለው ፍይዳ የጎላ በመሆኑ በትኩረት ሊሠራበት እንደሚገባ ነው የገለፁት ።

በክልሉ የስነ-ምግባር እና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን የስነ-ምግባር ትምህርት ሥርፀት ዳይሬክተር አቶ በፍቃዱ ዘለቀ የሀብት ምዝገባ እና ማሳወቅ ዓላማዎችን ጨምሮ በአዋጆችና ደንበኞች ላይ ትኩረት ያደረገ ስልጠና ሲሰጡ ሀብት ማሳወቅና ማስመዝገብ ብልሹ አሰራሮችን ለመከላከል የሚረዳ ስልት ነው ብለዋል ።

የአሰራር ሥርዓት ጥናት መሠረታዊ ሀሳቦችንና ሂደትን መከተል ሌላኛው ሙስናን ለመከላከል የሚያግዝ መሆኑን የገለፁት ደግሞ በክልሉ የስነ-ምግባር እና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን የስነምግባር አውታሮች ማስተባበሪያ ዳይረክተሬት ወ/ሮ ጥሩእሸት ደቦጭ ናቸው ።

ስልጠናው የኮሚሽኑ አዋጆችና መመሪያ ፣ ሙስናና የጥቅም ግጭት ፣ሙስናን መከላከል ፣በሀብት ማሳወቅና ምዝገባ ማካሄድ እንዲሁም የአሰራር ጥናት ላይ ትኩረት ያደረገ ነው ።