ለፍትሕ መከበር ሲባል በብዙ የጠበቃችሁን ተመልካቾቻችን፣ ሕግ አክብረን ፍትሕ ያገኘን በመሆኑ “ፍቅር እስከ መቃብር”ን በቅርቡ ይዘን እንመለሳለን!
የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ) “ፍቅር እስከ መቃብር” የተሰኘውን ድርሰት ወደ ፊልም ቀይሮ ከመሥራት ጋር በተያያዘ በፍርድ ቤት የቀረበበትን ክስ በሕግ አግባብ ተከራክሮ ረትቷል።
የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት “ፍቅር እስከ መቃብር”ን አስመልክቶ በኢቢሲ በኩል እንዲሁም በከሳሽ በኩል የቀረበውን የሰነድ ማስረጃ መርምሮ የከሳሽ ጥያቄን ሙሉ ለሙሉ ውድቅ ማደረጉን እና ከዛሬ ጥር 29 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ ተሰጥቶ የነበረው እግድ መነሣቱን በመጥቀስ ውሳኔ ሰጥቷል።
ፍርድ ቤቱ በዛሬው ዕለት የሰጠው ውሳኔ ኢቢሲ ከመነሻውም የ“ፍቅር እስከ መቃብር” ባለቤትነት መብቱን የገዛው ሕጋዊ መንገዱን ተከትሎ መሆኑን እንዲሁም የመጽሐፉ ደራሲ ክቡር ዶክተር ሐዲስ ዓለማየሁ በሕይወት እያሉ መብቱን በሽያጭ ያስተላለፉት ስለመሆኑ እና ኢቢሲ የ“ፍቅር እስከ መቃብር” ድርሰትን ወደ ፊልም ለመቀየር ሕጋዊ መብት ያለው መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው ሲሉ የሕግ ጉዳዩን የተከታተሉት በኢቢሲ የሕግ ነክ ጉዳዮች ዲፓርትመንት ኃላፊ ወ/ሮ መስከረም ዳግማዊ ገልጸዋል።
ኢቢሲ በሕግ የተቋቋመ ሀገራዊ ኃላፊነቱን በአግባቡ ሲወጣ የኖረ እና ያለ፤ የደራሲውን ሥራ በወጋየሁ ንጋቱ ትረካ ከፍ ያደረገ እና በዚህም በይፋ ደራሲው ያመሰገኑት ተቋም ነው።
አሁንም የተደረገው ያንኑ ሌጋሲ የሚያስቀጥል፣ የደራሲውን ሕልም የሚፈታ እና በሕጋዊ እና እውቅና ባለው ይሁንታቸው የተላለፈውን መብት መነሻ በማድረግ የሠራን በመሆኑ ፊልሙን በቅርቡ ለዕይታ የምናበቃ መሆኑን እንገልጻለን።
More Stories
በሚዛን ቴፒ ዩኒቨርስቲ ቴፒ ግቢ አዘጋጅነት የተካሄደው14ኛው ሀገር አቀፍ የምርምር ጉባኤ ተጠናቀቀ ።
ማዕከሉ ከተቋቋመ አጭር ጊዜ ውስጥ 21ሺ 5መቶ ቶን በላይ ቡና ለማዕከላዊ ገበያ ማቅረቡን በኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን የቴፒ ምርት ጥራት ምርምርና ሰርትፍኬሽን ማዕከል አስታወቀ።
አሜሪካ ከኢራን ጋር ባደረገችው ጦርነት 25 ቢሊየን ዶላር የሚጠጋ ገንዘብ አጣች