አብዛኞቻችን ከቤታችን የሚወጡ ቆሻሻዎችን በፍጥነት አውጥተን ለመጣል እንቸኩላለን፤ በቤታችን ውስጥ ለጥቂት ጊዜ እንኳ እንዲቆዩ አንፈልግም።
በዴንማርክ የሚኖረው የሪሳይክል አርቲስት ቶማስ ዳምቦ ግን አስተሳሰባችንን ሙሉ በሙሉ የሚቀይር ድንቅ ስራ እየሰራ ይገኛል።
ይህ አርቲስት ሰዎች አውጥተው የጣሏቸውን ቆሻሻዎች መልሶ ጥቅም ላይ በማዋል መላውን ዓለም ማስደነቅ ችሏል።
የ46 ዓመቱ አርቲስት ቶማስ ዳምቦ በዓለም ዙሪያ በሚገኙ ደኖች፣ ተራሮችና ውብ የተፈጥሮ ስፍራዎች ውስጥ በሚያቆማቸው ግዙፍ የእንጨት ቅርጻ ቅርጾች በሰፊው ይታወቃል።
እነዚህ ቅርጻ ቅርጾች “ትሮል” (Troll) የሚባሉ በስካንዲኔቪያ አፈ ታሪክ የሚታወቁ ግዙፍ ፍጥረታትን የሚወክሉ ሲሆን፣ አርቲስቱ በእነዚህ ግዙፍ ምስሎች አማካኝነት ስለ አካባቢ ጥበቃ እና ቆሻሻን መልሶ ጥቅም ላይ ስለማዋል ለአለም ጠቃሚ መልዕክቶችን ያስተላልፋል።
ይህ የጥበብ ጉዞ የተጀመረው አርቲስቱ በፈረንጆቹ 2014 በዴንማርክ የሙዚቃ ፌስቲቫል ላይ ሁለት የትሮል ቅርጻ ቅርጾችን ከሠራ በኋላ ሲሆን፣ ባለፉት 10 ዓመታት ውስጥ ብቻ በ19 ሀገራት ውስጥ ወደ 200 የሚጠጉ አስደናቂ ሥራዎችን ለዓለም አበርክቷል።
አሁን ደግሞ ይበልጥ በሚያጓጓ መልኩ የመጀመሪያውን የሙዚየም ትርኢት ለተመልካች አቅርቧል።
የእነዚህ ሥራዎች ዋና ዓላማ ሰዎች በጥበብ አያያዝና በፍጆታ ዕቃዎች አጠቃቀም ላይ ያላቸውን አመለካከት እንዲቀይሩ ማስተማር ነው።
ቅርጻ ቅርጾቹ በአብዛኛው ከተጣሉ የእንጨት ርብራቦች፣ ከአሮጌ የቤት ዕቃዎችና ከዊስኪ በርሜሎች የተሠሩ ሲሆን፣ በአዲሱ የሙዚየም ኤግዚቢሽን ውስጥ ደግሞ የተጣሉ ኤሌክትሮኒክስ፣ ካርቶኖችና አልባሳት ጭምር ጥቅም ላይ ውለዋል።
ይህ መረጃ እንደሚያሳየው፣ እኛ “ቆሻሻ” ብለን የምንጥለው ነገር በፈጠራ እጅ ሲገባ ለአካባቢ ጥበቃ ትልቅ ትምህርት የሚሰጥ እንዴት ያለ ድንቅ ጥበብ መሆን እንደሚችል ቶማስ ዳምቦ በተግባር አሳይቷል።
More Stories
የዓለማችን እጅግ አስገራሚ ሠርጎች
በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የተደረሰው ረቂቅ የሰላም ስምምነት ለሆርሙዝ ሰርጥ ደኅንነት…
የአመጋገብ ሥርዓታችንን ለመቀየር የሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር ተጠናክሮ ይቀጥላል- ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ