May 23, 2026

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

በ24 ሰዓት ውስጥ 25 መርከቦች በሆርሙዝ ሰርጥ አልፈዋል – ኢራን

የኢራን አብዮታዊ ዘብ ባለፉት 24 ሰዓት ውስጥ 25 የንግድ መርከቦች በሆርሙዝ ሰርጥ አልፈዋል አለ፡፡

የአብዮታዊ ዘቡ የባህር ኃይል እንዳስታወቀው÷ ኢራን ያስቀመጠችውን የቁጥጥር እና የደህንነት መስፈርቶችን በማሟላት በሆርሙዝ ሰርጥ የንግድ መርከቦች እየተላለፉ ነው፡፡

የነዳጅ እና እቃ ጫኝ መርከቦችን ጨምሮ በአጠቃላይ 25 የንግድ መርከቦች በአንድ ቀን ውስጥ በሆርሙዝ ሰርጥ መተላለፋቸውን ጠቅሶ፤ ኢራን በሰርጡ የምታደርገው ቁጥጥር መቀጠሉን ገልጿል።

እስራኤል እና አሜሪካ ጥቃት መፈጸማቸውን ተከትሎ ኢራን በፈረንጆቹ 2026 የካቲት ወር የሆርሙዝ ሰርጥን ሙሉ በሙሉ መዝጋቷ ይታወሳል፡፡

እንደ ፕሬስ ቲቪ ዘገባ፤ የኢራን አብዮታዊ ዘብ በሆርሙዝ ሰርጥ እያደረገ ባለው ቁጥጥር የሩሲያ እና ቻይና መርከቦች ቅድሚያ ተሰጥቷቸዋል።

ይህ የሆነው ሀገራቱ የኢራን አጋሮች በመሆናቸው የተገለጸ ሲሆን፤ በተቃራኒው የኢራን ወዳጅ ባልሆኑ ሀገራት መርከቦች ላይ ቀረጥን ጨምሮ ሌሎች ፍተሻዎች እየተደረገባቸው ነው።

በተለይም አብዮታዊ ዘቡ የኢራን ጠላቶች እና አጋሮቻቸው የሆኑ ሀገራት መርከቦችን የባለቤታቸውን እና የግንኙነት መስመራቸውን የመርመር እና የመርከቦችን የጭነት ይዘት በተመለከተ አካላዊ ፍተሻን ያደርጋል ነው የተባለው፡፡

ኢራን ያስቀመጠችውን ቁጥጥር ተከትሎ ዓለም አቀፍ የመርከብ ኩባንያዎች በሆርሙዝ ሰርጥ ላይ ያለውን ደህንነት ለማረጋገጥ ከኢራን ጋር በግል እየመከሩ ይገኛሉ።