ኢትዮጵያ የአፍሪካ ኑክሌር ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ የበይነ መንግሥታት የትብብር ስምምነት ሊቀመንበር ሆና ተመርጣለች።ከመስከረም 6 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ በኦስትሪያ ቪዬና ሲካሄድ የቆየው 68ኛው የዓለም የአቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ዓመታዊ ጉባኤ በዛሬው ዕለት ተጠናቋል፡፡ በኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) የተመራው የኢትዮጵያ ልዑክ በጉባኤው ላይ ተሳትፎ ያደረገ ሲሆን የተለያዩ የጎንዮሽ ውይይቶችንም አድርጓል።ኢትዮጵያ ከጉባኤው ጎን ለጎን የአፍሪካ ኑክሌር ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ የበይነ መንግሥታት የትብብር ስምምነት (AFRA) ሊቀመንበር ሆና ተመርጣለች።ኢትዮጵያ ሊቀ መንበርነቷን ከአልጄሪያ የተረከበች ሲሆን የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) በሊቀ መንበርነት ተመርጠዋል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ በአንድ ዓመት የሊቀ መንበርነት ቆይታዋ በአፍሪካ እያደገ እና እየሰፋ የመጣውን የኑክሌር ሳይንስ እና ቴክኖሎጂን ለሰላማዊ አላማ እንዲውል አበክረው እንደሚሰሩ ገልጸዋል።ቴክኖሎጂው በተለይም ለጤና፣ ለግብርና፣ ለማዕድን ልማት፣ ለአካባቢ ጥበቃ፣ ለኃይል ምንጭነት፣ለኢንዱስትሪ እና ሌሎች ዘርፎችን እንዲደግፍ በትኩረት እንደሚሰራ መናገራቸውን ከሚኒስቴሩ የተገኘው መረጃ ያመላክታል፡፡
EBC
More Stories
ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ፡- በብዝኃነት ላይ የተመሠረተ ወል ትርክትን የመገንባት ጉዞ
የወሳኝ ኩነቶች ምዝገባ ስራ ስኬታማነት ላይ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በቅንጅት ሊሰሩ ይገባል ተባለ
በብልፅግና ፓርቲ የሚመራው የመደመር መንግስት ያደሩ በርካታ የልማት ጥያቄዎችን ከመፍታት ባሻገር አዳዲሶቹን ጀምሮ በማጠናቀቅ የሕዝቡን ተጠቃሚነት እያረጋገጠ እንደሚገኝ አቶ ፍቅሬ አማን ገለጹ።