ቴሒራን ማስጠንቀቂውን የሰጠችው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ የአሜሪካ ጦር ኃይል ኢራንን “ወደ ድንጋይ ዘመን” እንደሚመልሳት መዛታቸውን ተከትሎ ነው።
ኻታም አል-አንቢያ ተብሎ የሚጠራው የኢራን ጦር ሠራዊት የዘመቻዎች ዕዝ “ይህ ጦርነት እስከ ውርደታችሁ፤ እስከ ውድቀታችሁ፣ ዘላቂ እና የተረጋገጠ ጸጸታችሁ እና እጃችሁን እስክትሰጡ ይቀጥላል” በማለት እንዳስጠነቀቀ የኢራን ብሔራዊ የቴሌቭዥን ጣቢያ ዘግቧል።
የዶናልድ ትራምፕ ዛቻ የተሰማው አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ሥለከፈቱት ጦርነት ለአሜሪካ ሕዝብ ትላንት ረቡዕ ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት ነው። ስለ ጦርነቱ በመገናኛ ብዙኃን እና በማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች አስተያየት ሲሰጡ የቆዩት ትራምፕ በይፋ ለሀገራቸው ሕዝብ ማብራሪያ ሲሰጡ አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ዘመቻ ከከፈቱ ወዲህ የመጀመሪያቸው ነው።
ፕሬዝደንቱ በንግግራቸው እንደ ከዚህ ቀደሙ ሀገራቸው ጦርነቱን እያገባደደች እንደምትገኝ ተናግረዋል።የአሜሪካ “ቁልፍ ስልታዊ ዓላማዎች ሊጠናቀቁ ተቃርበዋል” ሲሉ ተደምጠዋል። ባለፈው አንድ ወር ገደማ በተወሰዱ እርምጃዎች የኢራን “ሚሳይሎች እና ድሮኖች የማስወንጨፍ አቅም በከፍተኛ ሁኔታ ቀንሷል። የጦር መሣሪያ ፋብሪካዎቻቸው እና የሮኬት ማስወንጨፊያዎቻቸው ወደ ፍርስራሾች እየተቀየሩ ነው” ሲሉ ተናግረዋል።
የኢራን “ባሕር ኃይል የለም፤ አየር ኃይላቸው ፈራርሷል” ያሉት ትራምፕ “መሪዎቻቸው ሞተዋል” ሲሉ ተደምጠዋል።
“በሚቀጥሉት ሁለት እና ሦስት ሣምንታት በኃይል እንደበድባቸዋል። ወደ ሚገባቸው የድንጋይ ዘመን እንመልሳቸዋልን” በማለት የዛቱት የ79 ዓመቱ ፕሬዝደንት “ውይይቶች ቀጥለዋል” ሲሉ ተደምጠዋል። ትራምፕ “ሥራውን እንጨርሰዋለን፤ በፍጥነት እንጨርሰዋለን፤ ለመጨረስ በጣም እየተቃረብን ነው” ብለዋል።
ትራምፕ የኢራን ወታደራዊ አቅም መዳከሙን ቢናገሩም እስራኤል ግን ዛሬ ሐሙስ በኢራን የሚሳይል ጥቃት እንደተፈጸመባት ገልጻለች። የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች በበኩሏ የአየር መከላከያዋ በድጋሚ ለሚሳይሎች እና የድሮን ሥጋቶች ምላሽ እየሰጠ እንደሆነ አሳውቃለች።
ኻታም አል-አንቢያ ተብሎ የሚጠራው የኢራን ጦር ሠራዊት የዘመቻዎች ዕዝ ማዕከላዊ ዋና ጽህፈት ቤት ቃል አቀባይ ኢብራሒም ዞልፋቃሪ አሜሪካ እና እስራኤል የኢራን ወታደራዊ አቅምን በተመለከተ የሰሩት ትንተና “ጎዶሎ” እንደሆነ ገልጸዋል።
More Stories
የተደበቁ ሀብቶች በአደባባይ፡ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ አዳዲስ የቱሪዝም ገጽታዎች
ትራምፕ በኢራን ላይ እንፈጽማለን ላሉት ጥቃት ያስቀመጡትን ቀነ ገደብ በድጋሚ አራዘሙ
በ48 ነጥብ 8 ሚሊየን ዶላር ወጪ 500 ሺህ ዘመናዊ ቆጣሪዎችን ለመግጠም እየተሰራ ነው