March 12, 2026

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

በክልሉ ከሚገኙ ቡና አቅራቢ ነጋዴዎች ጋር በወቅታዊ የቡና ገበያ ላይ በቦንጋ ከተማ ምክክር እየተደረገ ነዉ

የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ዝቦች ክልል ከሚገኙ አቅራቢ ነጋዴዎች ጋር በወቅታዊ የቡና ገበያ ነባራዊ ሁኔታን አስመልክቶ በቦንጋ ከተማ ምክክር እያደረገ ነው።

በምክክሩ ቡና  ያከማቹ አምራቾች እና ነጋዴዎች በአፋጣኝ ለገበያ እነዲያወጡ አቅጣጫ ተቀምጧል።

በመድረኩ የተገኙት የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ታጋይ ኑሩ በኢትዮጵያ ከ30 ሚሊየን በላይ ዜጎች የኑሮ መሠረት ከቡና ጋር የተቆራኘ ነው ብለዋል።

በቡና የግብይት ስርዓት ውስጥ የደላላዎች ጣልቃ ገብነት በመኖሩ የአምራችና አቅራቢ ነጋደዎች የመረጃ ልውውጥ ክፍተት ለዘርፉ ማነቆ መሆኑን አንስተዋል።

ቡና የሀገር ኢኮኖሚ ምንጭ እንደመሆኑ ከግብይት ስርዓት ውጪ ያከማቹ አካላት በአፋጣኝ በእጃቸው ያለውን ምርት ለገበያ ማቅረብ አሳስበዋል።

የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ  ሕዝቦች ክልል መንግስት ርዕሰ መስተዳድር አማካሪ አቶ ሰብስቤ ሻዎኖ በበኩላቸው ቡና የኤክስፖርት ምርት እንደመሆኑ የሽያጭ ዋጋ በዓለም ገበያ እንደሚወሰን ተናግረዋል።

ቡናን ከተፈቀደው ጊዜ በላይ በመጋዘን ማቆየት ለጥራት ጉድለት ከማጋለጡም ባለፈ በሚለዋወጠው የአለም ገበያ ምክንያት ላልተፈለገ ኪሳራ እንዳይዳረጉ ከባለስልጣን መስሪያ ቤቱ የሚተላለፉ የአሠራር መመሪያዎችንና መረጃዎችን ተግባራዊ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል ብለዋል።

ቡናን በወቅቱ አዘጋጅቶ ለማቅረብ በኢንዱስትሪዎች የነዳጅ እጥረት ኤክፖርተሮች ምርት ከተረከቡ በኋላ ሙሉ ክፍያ አለመፈጸም ችግሮች መኖራቸውን ተሳታፊዎች አንስተዋል።

ከደረሰኝ ህትመት ጋር ተያይዞ እንደ ሀገር በአንድ ድርጅት ብቻ እንዲታተም መደረጉ ለከፍተኛ መጉላላት እየዳረገ በመሆኑ አማራጭ እድሎች እንዲመቻቹ ጠይቀዋል።

በሌላ መልኩ የጫኚና አውራጅ ሠራተኞች የጭነት ትራንስፖርት ዋጋ መጨመር ምርትን በአፋጣኝ ገበያ ለማቅረብ ተግዳሮት በመሆኑ  የሚመለከታቸው አካላት ለዘርፉ አስፈላጊውን እገዛ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል ሲል ቦንጋ ኤፍ ኤም ዘግቧል።