February 4, 2026

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

አስተማማኝ ሽግግር እስኪካሄድ ድረስ አሜሪካ ቬንዙዌላን ትመራለች’ፕሬዝዳንት ትራምፕ

ማሻ፣ ታህሳስ 26/2018 ዓ/ም (ማሻ ኤፍኤም 103.8) ቬንዙዌላ ውስጥ ጥቃት እንዲፈጸም አዝዘው ፕሬዝዳንቱን በቁጥጥር ሥር ያዋሉት ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተማማኝ ሁኔታ እስኪፈጠር ድረስ አሜሪካ አገሪቱን እንደምትመራ ተናገሩ።

ቬኒዙዌላ ላይ ድንገተኛ የኮማንዶ ጥቃት በመፈጸም አገሪቱ መሪ በአሜሪካ እጅ መግባታቸውን በተመለከተ ፕሬዝንት ትራምፕ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ “አስተማማኝ፣ ተገቢ እና ሕጋዊ ሽግግር እስኪካሄድ ድረስ ቬንዙዌላን አሜሪካ ታስተዳድራለች” ሲሉ በኩራት ተናግረዋል።

በጋዜጣዊ መግለጫቸው ላይ ትራምፕ የአገሪቱን የነዳጅ ሀብት በተመለከተም ትላልቅ የአሜሪካ ኩባንያዎች ወደ ቬንዙዌላ በመግባት መሠረተ ልማቶቿን መልሶ በመጠገን “ለአገሪቱ ገቢ ማስገኘት ይጀምራሉ” ሲሉ ተናግረዋል።

ከፍተኛ የነዳጅ ዘይት ሀብት ያላት ቬንዙዌላ ባለፉት ሳምንታት ምርቷን ወደ ውጭ እንዳትልክ በአሜሪካ እንቅፋት ተፈጥሮባት ቆይቷል። ነዳጅ ጫኝ መርከቦችም ከነጭነታቸው በአሜሪካ ቁጥጥር ሥር ወድቀዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ፕሬዝዳንት ትራምፕ በወታደሮቻቸው ቁጥጥር ሥር የገቡትን የፕሬዝዳንት ማዱሮን ምሥል አጋርተዋል።

ምንጮች በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር ለሆነው ሲቢኤስ እንዳረጋገጡት ማዱሮን ያሳፈረው የአሜሪካ ጦር ሠራዊት አውሮፕላን በሰዓታት ውስጥ ኒው ዮርክ ያርፋል።

በዕጽ እና በጦር መሳሪያ ወንጀሎች ክስ የተመሠረተባቸው ኒኮላስ ማዱሮ አሜሪካ እንደደረሱ ጦር ሠራዊቱ ለፌደራል መንግሥቱ ባለሥልጣናት አሳልፈው እንደሚሰጧቸው እና በሚቀጥለው ሳምንትም ኒው ዮርክ ውስጥ ከሚገኝ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ ተብሎ ይጠበቃል።

#(BBC)