February 4, 2026

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

ኢራን ሰላማዊ ተቃዋሚዎችን የምትገድል ከሆነ አሜሪካ ጣልቃ በመግባት እንደምታድናቸው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ገለጹ።

ማሻ፣ ታህሳስ 24/2018 ዓ/ም (ማሻ ኤፍኤም 103.8) በኢራን የተለያዩ ከተሞች የኑሮ ውድነትን እና የአገሪቱ ገንዘብ የመግዛት አቅም ማሽቆልቆሉን በመቃወም በርካታ ሰዎች አደባባይ ወጥተው ድምጻቸውን ማሰማት ከጀመሩ ቀናት ተቆጥረዋል።

በዚህም ሳቢያ ትራምፕም ኢራን ተቃዋሚዎችን በጭካኔ በጥይት የምትገድል ከሆነ “እርምጃ ለውሰደ ዝግጁ ነን” በማለት በትሩዝ የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ አስፍረዋል።

ትራምፕ ይህንን ያሉት ከሦስት ዓመት ወዲህ በኢራን ውስጥ ያጋጠመ ነው በተባለው የአሁኑ ተቃውሞ በርካታ ሰዎች መገደላቸውን የሚያመለክቱ ዜናዎች መውጣታቸውን ተከትሎ ነው።

በተቃዋሚዎች እና በመንግሥት ፀጥታ ኃይሎች መካከል ግጭት የተቀሰቀሰው ባለፈው ዕሁድ ባለሱቆች በፍጥነት እየጨመረ ያለውን የዋጋ ንረት እና መንግሥት እያሽቆለቆለ ያለውን የአገሪቱን የመገበያያ ገንዘብ ለመታደግ ምንም አላደረገም በሚል ተቃውሞ ካሰሙ በኋላ ነው።

ፕሬዝዳንት ትራምፕ በመጀመሪያው የሥልጣን ዘመናቸው ከኢራን ጋር ከተደረሰው የኒውክሌር ስምምነት ከወጡ በኋላ ተነስቶላት የነበረውን ማዕቀብን በአውሮፓውያኑ 2018 መልሰው ስለጣሉባት የኢራን ምጣኔ ሀብት ችግር ውስጥ ገብቶ ቆይቷል።

በኢራን የተለያዩ ግዛቶች ውስጥ የሚካሄደው ተቃውሞ እየተባባሰ የቀጠለ ሲሆን፣ የፀጥታ ኃይል አባላትን ጨምሮ የሰው ሕይወት እያለፈ መሆኑ ተዘግቧል።