ማሻ ፣ የግንቦት 25፣ 2017 (ማሻ ኤፍ ኤም) በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የጤናው ዘርፍ አርበኝነት ለሀገር ዕድገት በሚል መርህ ቃል በቦንጋ ከተማ ሲካሄድ የቆየው ክልል አቀፍ ውይይት ተጠናቋል ።
በውይይት መድረኩ ላይ የተገኙት የክልሉ ርዕስ መስተዳድር ዶክተር ኢንጅነር ነጋሽ ዋጌሾ እንደገለፁት የክልሉ ጤና ባለሙያዎችና የጤና ተቋማት አመራሮች ያሳዩት አቋም ለህዝባቸው ያለው ውግንና እና ለሙያቸው ያላቸውን ክብር ያረጋገጡበት ነው።
መንግስት ጥያቄዎቹን በጥናት ላይ ተመስርቶ የሀገሪቱ አቅም በፈቀደው መጠን ምላሽ ለመስጠት እንደሚሰራም አረጋግጠዋል።
የክልሉ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ሃላፊ አቶ ፍቅሬ አማን በበኩላቸው መንግስት የተጠቆሙ ጉድለቶችን ለማረም የጀመራቸውን ተግባራት አጠናክሮ እንደሚያስቀጥል ተናግረዋል።
የመወያያ ሰነድ ለተሳታፊዎች ያቀረቡት በክልሉ ጤና ቢሮ ሃላፊ አቶ ኢብራሂም ተማም እንደገለፁት መንግስት የማሻሻያ እርምጃዎችን ከመወሰድ ጅምሮ የጤና ልማት ስራን የሚያሻግሩ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን አስረድተዋል ።
የውይይቱ ተሳታፊዎች የህክምና ግብአቶች እጥረት ማህበረሰቡ የተሟላ አገልግሎት እንዳያገኝ ተፅዕኖ እያሳደረ እንደሆነ ገልፀው መንግስት ለችግሩ ትኩረት በመስጠት መቅረፍ እንዳለበት ጠይቀዋል ።
ከጥቅማጥቅም ጋር የተያያዙ ጥያቄዎችም በስፋት የተነሱ ሲሆን መንግስት ባለሙያዎችን ለማድመጥ ያሳየውን ዝግጁነትን ተሳታፊዎች አድንቀዋል ።
በክልሉ 14 ሆስፒታሎችና 127 ጤና ጣቢያዎች አገልግሎት እየሰጡ ሲሆን የጤና ኬላዎችንም ማጠናከር እንደሚገባ በመድረኩ ተጠቁሟል ።
በወንድሙ ካኪሎ
More Stories
በክልሉ ሁሉም ቀበሌዎች የተቀናጀ 2ኛ ዙር የልጅነት ልምሻ በሽታ መከላከያ ክትባት ከግንቦት 22-25/2017 ዓ.ም እንደሚሰጥ ተገለጸ።
ከጤና ሚኒስቴር እና ከኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት MPox አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ
ለ11 ሚሊየን ህፃናት የኩፍኝ ክትባት ተሰጠ