ለቀጣይ ቅዳሜ በሮም ሊካሄድ ቀጠሮ ተይዞለት የነበረው አራተኛው ዙር የኢራን እና አሜሪካ የኑክልየር ድርድር ላልተወሰነ ጊዜ ተራዝሟል፡፡
ሁለቱን ወገኖች እያደራደረቻቸው ያለችው ኦማን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ባድር ቢን ሃማድ አል-ቡሳይዲ መርሐ ግብሩ የዘገየው ‘በሎጂስቲክ ምክንያቶች ነው’ ቢሉም፣ አንዳንድ ወገኖች በሀራቱ መካከል እየተካረረ በመጣው ውጥረት ምክንያት ሊሆን እንደሚችል ግምታቸውን አስቀምጠዋል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አራተኛውን ድርድር እ.አ.አ ለሜይ 3 ቀን 2025 በሮም እንዲካሄድ ታስቦ የነበረ ቢሆንም አለመሳካቱን ጠቅሰው፣ ቀጣዩን የድርድር ጊዜ በቅርቡ እንደሚያሳውቁ ተናግረዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕን ጨምሮ የአሜሪካ ባለሥልጣናት ኢራን የየመኑን ሁቲ መደገፍ እና ኑክልየርን ማበልፀግ በመቀጠሏ ተጨማሪ ማዕቀቦችን ሊጥሉባት እንደሚችሉ ሲያሳስቡ፣ ኢራን በበኩሏ ኑክልየርን ለሰላማዊ የኃይል ምንጭ ብቻ እያበለፀገች እንደሆነ ገልጻለች፡፡
አሜሪካ በነዳጅ ምርቶቿ ላይ የጣለችው ማዕቀብም ሀገራቱ መተማመን ላይ እንዳይደርሱ ምክንያት እየሆነ መሆኑን ኢራን ጠቅሳለች፡፡
የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ ጉዳዩን አስመልክተው በሰጡት አስተያየት ድርድሩ የዘገየው በኦማን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጥያቄ ነው ብለዋል።
ቃል አቀባዩ አክለውም ሀገራቸው ከአሜሪካ ጋር ፍትሃዊ እና ዘላቂ ስምምነት ላይ ለመድረስ ቁርጠኛ መሆኗን አጽንኦት ሰጥተው መግለጻቸውን የዘገበው አልጀዚራ ነው።
More Stories
ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ከዳያስፖራው ማህበረሰብ አጀንዳ ማሰባሰብ ጀመረ
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ምክር ቤት የዘርፍ ቋሚ ኮሚቴዎች የ2017 በጀት አመት የአስፈፃሚ አካላት አፈፃፀም ግምገማ መድረክ እየተካሄደ ይገኛል።
ማህበረሰቡ በከባድ ዝናብ ምክንያት ከሚከሰቱ አደጋዎች እንዲጠነቀቅ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን አሳሰበ።