ለፍትሕ መከበር ሲባል በብዙ የጠበቃችሁን ተመልካቾቻችን፣ ሕግ አክብረን ፍትሕ ያገኘን በመሆኑ “ፍቅር እስከ መቃብር”ን በቅርቡ ይዘን እንመለሳለን!
የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ) “ፍቅር እስከ መቃብር” የተሰኘውን ድርሰት ወደ ፊልም ቀይሮ ከመሥራት ጋር በተያያዘ በፍርድ ቤት የቀረበበትን ክስ በሕግ አግባብ ተከራክሮ ረትቷል።
የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት “ፍቅር እስከ መቃብር”ን አስመልክቶ በኢቢሲ በኩል እንዲሁም በከሳሽ በኩል የቀረበውን የሰነድ ማስረጃ መርምሮ የከሳሽ ጥያቄን ሙሉ ለሙሉ ውድቅ ማደረጉን እና ከዛሬ ጥር 29 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ ተሰጥቶ የነበረው እግድ መነሣቱን በመጥቀስ ውሳኔ ሰጥቷል።
ፍርድ ቤቱ በዛሬው ዕለት የሰጠው ውሳኔ ኢቢሲ ከመነሻውም የ“ፍቅር እስከ መቃብር” ባለቤትነት መብቱን የገዛው ሕጋዊ መንገዱን ተከትሎ መሆኑን እንዲሁም የመጽሐፉ ደራሲ ክቡር ዶክተር ሐዲስ ዓለማየሁ በሕይወት እያሉ መብቱን በሽያጭ ያስተላለፉት ስለመሆኑ እና ኢቢሲ የ“ፍቅር እስከ መቃብር” ድርሰትን ወደ ፊልም ለመቀየር ሕጋዊ መብት ያለው መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው ሲሉ የሕግ ጉዳዩን የተከታተሉት በኢቢሲ የሕግ ነክ ጉዳዮች ዲፓርትመንት ኃላፊ ወ/ሮ መስከረም ዳግማዊ ገልጸዋል።
ኢቢሲ በሕግ የተቋቋመ ሀገራዊ ኃላፊነቱን በአግባቡ ሲወጣ የኖረ እና ያለ፤ የደራሲውን ሥራ በወጋየሁ ንጋቱ ትረካ ከፍ ያደረገ እና በዚህም በይፋ ደራሲው ያመሰገኑት ተቋም ነው።
አሁንም የተደረገው ያንኑ ሌጋሲ የሚያስቀጥል፣ የደራሲውን ሕልም የሚፈታ እና በሕጋዊ እና እውቅና ባለው ይሁንታቸው የተላለፈውን መብት መነሻ በማድረግ የሠራን በመሆኑ ፊልሙን በቅርቡ ለዕይታ የምናበቃ መሆኑን እንገልጻለን።
More Stories
ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ከዳያስፖራው ማህበረሰብ አጀንዳ ማሰባሰብ ጀመረ
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ምክር ቤት የዘርፍ ቋሚ ኮሚቴዎች የ2017 በጀት አመት የአስፈፃሚ አካላት አፈፃፀም ግምገማ መድረክ እየተካሄደ ይገኛል።
ማህበረሰቡ በከባድ ዝናብ ምክንያት ከሚከሰቱ አደጋዎች እንዲጠነቀቅ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን አሳሰበ።