የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከፈረንሳይ፣ኮሪያና ከዓለም አቀፍ የልማት ማህበር ጋር የተደረጉ አራት የብድር ስምምነቶችን መርምሮ አጽድቋል፡፡
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 12ኛ መደበኛ ስብሰባው በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ እና በኮሪያ ኤክስፖርት-ኢምፖርት ባንክ መካከል ለህክምና መሳሪያዎች አቅርቦት ፕሮጀክት ምዕራፍ-2 እና ለብሔራዊ የኤሌክትሪክ ኃይል ማስተላለፊያ ሥርዓት ማስፋፊያ ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ የተደረገውን የብድር ስምምነት አጽድቋል።
በተጨማሪም በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክና በፈረንሳይ የልማት ኤጀንሲ መካከል ለታዳሽ፣ የተቀናጀ፣ዘላቂ ኃይልና ዲጂታላይዜሽን ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ የብድር ስምምነትን አጽድቋል።
በሶስተኛነትም በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክና በዓለም አቀፍ የልማት ማኅበር መካከል ለከተማ ልማታዊ ሴፍትኔትና ሥራ ፈጠራ ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ የብድር ስምምነትን አጽድቋል፡፡
የጉምሩክ አዋጅን እንደገና ለማሻሻል የቀረበውን ረቂቅ መርምሮ ለፕላን፣በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ መምራትም ምክር ቤቱ በመደበኛ ስብሰባ ከመከረባቸው ጉዳዮች አንዱ ነው።
በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጄ፤ የሕክምና መሳሪያዎች አቅርቦት ፕሮጀክት ምዕራፍ-2 ማስፈጸሚያ የብድር ስምምነቱ ከሀገሪቱ ዲፕሎማሲያዊ ትብብር ጋር የተጣጣመ መሆኑን ገልጸዋል።
አነስተኛ ወለድ ምጣኔ ያለው የብድር ስምምነቱም የጤና አገልግሎት ተደራሽነትን ለማስጠበቅ በሚደረገው ጥረት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያደርግ ተናግረዋል።
በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር)፤ ስምምነቶቹ ዘላቂ የልማት ግቦችን የሚያሳልጡና ከኢትዮጵያ የብድር አስተዳደር ስርዓት ጋር የተጣጣሙ ናቸው ብለዋል።
የጉምሩክ አዋጅን እንደገና ለማሻሻል የቀረበው ረቂቅ አዋጅም ተቋሙ ወቅቱን የዋጀና የተሳለጠ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል።
የምክር ቤቱ አባላት በብድር ስምምነቶችና የጉምሩክ አዋጁን እንደገና ለማሻሻል በቀረበው ረቂቅ ላይ በሰጡት አስተያየት፤በብድር የሚገኝ ሀብት ለታለመለት ዓላማ እንዲውል ጥብቅ ቁጥጥር ማድረግ ይገባል ብለዋል።
የብድር ስምምነቶቹም የህብረተሰቡን የልማት ጥያቄ ለመመለስ ትልቅ አቅም እንደሚሆኑም ገልጸዋል፡፡
የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ሰመሪታ ሰዋሰው፤በብድር ስምምነት የተገኙ ሃብቶች ላይ ጥብቅ የፕሮጀክት አፈፃጸም ቁጥጥር በማድረግ ለዜጎች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እንዲውሉ ይደረጋል ብለዋል።
የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን በበኩላቸው፤ የብድር ስምምነቶቹ የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ለዘላቂ የልማት ግቦች ውጤታማነት ጉልህ ሚና እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡
More Stories
ወድቀህ ተነሣ እንደ መገጭ ግድብ፦ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
ምንም እንኳ የዓለም አቀፍ አቅርቦት ቢፈታተነንም፣ በበልግ ዝናብ ውጤታማ መሆን ይቻላል፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ( ዶ/ ር)
አሜሪካና ኢራን ንግግርን በተመለከተ ያንጸባረቁት ተቃራኒ ሃሳብና የነዳጅ ዋጋ ዳግም መናር …