ማሻ፤ የካቲት 13/2018 ዓ/ም (ማሻ ኤፍ ኤም 103.8) በሸካ ዞን ገቢዎች መምሪያ አዘጋጅነት ለዞን፣ ለከተማና ለወረዳ የገቢ ተቋማት ፈፃሚዎች በሥነ-ምግባር እና አገልግሎት አሰጣጥ ዙሪያ ያተኮረ የመገምገሚያ ኦሬንቴሽን መድረክ በቴፒ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።
የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ምክትል ኃላፊ ወ/ሮ ትዕግስት በላይ በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፤ የገቢ ተቋሙ የዞኑንና የክልሉን የልማት ፍላጎት ለማሟላት ከፍተኛ ድርሻ ያለው ቢሆንም፣ አሁንም በየደረጃው በሚታዩ ችግሮች ምክንያት ያለውን አቅም (ፖቴንሻል) ሙሉ በሙሉ መጠቀም አልተቻለም።
በአመራሩና በፈፃሚው ዘንድ የሚታዩ የሥነ-ምግባር ክፍተቶችን በመቅረፍ ውጤታማ የገቢ አሰባሰብ ሥርዓት መዘርጋት የመድረኩ ዋና ዓላማ መሆኑን ገልጸዋል።
እንደ ወ/ሮ ትዕግስት ገለጻ፤ በክልሉ በየዓመቱ ከ4 ቢሊዮን እስከ 18 ቢሊዮን ብር የመሰብሰብ አቅም ቢኖርም፣ አሁን ላይ እየተሰበሰበ ያለው ግን ከዚህ በታች ነው።
በአሁኑ ወቅት ክልሉ የራሱን ወጪ እስከ 64% መሸፈን የቻለ ሲሆን፣ ቀሪውን 36% ለመሸፈን የተቀናጀ ጥረት እንደሚያስፈልግና ለዚህም በትኩረት እየተሠራ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።
የሸካ ዞን ገቢዎች መምሪያ ኃላፊ አቶ በላቸው በቀለ በበኩላቸው፤ መድረኩ በየተቋማቱ የሚስተዋሉ የሥነ-ምግባርና አጠቃላይ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በመለየት መፍትሄ ለማስቀመጥ ያለመ መሆኑን ገልጸዋል።
ተቋማዊ አቅምን በማጠናከር ከተከሰቱ ችግሮች በመውጣት፣ የዞኑን የልማት ፍላጎት ሊደግፍ የሚችል ቀልጣፋ የገቢ አሰባሰብ ሥርዓት መገንባት አስፈላጊ መሆኑንም አስገንዝበዋል።
በመድረኩ ላይ የሸካ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አበበ ማ፣ የዞኑ መንግሥት ዋና ተጠሪ አቶ አለማየሁ አለሙን ጨምሮ የመንግሥት ተጠሪዎች፣ የወረዳ አስተዳዳሪዎች፣ የከተማ ከንቲባዎች፣ የገቢዎች ጽሕፈት ቤት ኃላፊዎችና ፈፃሚዎች ተገኝተዋል። ዘገባው የዞኑ መ/ኮ ነው
More Stories
ዋሽግተን-ጠቅላይ ፍርድ ቤት የትራምፕን የቀረጥ ጭማሪ ደንብ ዉድቅ አደረገ
ኢትዮጵያ ከቱሪዝም ዘርፉ 2.6 ቢሊዮን ብር ገቢ አገኘች
በሸካ ዞን ቴፒ ከተማ አስተዳደር የተጀማመሩ የልማት እንቅስቃሴዎች ህዝቡንና መንግስትን የሚያስተሳስሩ በመሆናቸው ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል