February 16, 2026

Masha Fm Woreda to World

Woreda to World

የአፍሪካ ህብረት እና የአፍሪካ ልማት ባንክ አጋርነታቸውን ለማደስ ቁርጠኛ መሆናቸውን ገለጹ

ማሻ፤ የካቲት 9/2018 ዓ/ም (ማሻ ኤፍ ኤም 103.8) የአፍሪካ ህብረት እና የአፍሪካ ልማት ባንክ የአህጉሪቱን የፋይናንስ መዋቅር ማጠናከርን ጨምሮ በተለያዩ መስኮች ያላቸውን አጋርነት በአዲስ መልክ ለማደስ እንደሚሰሩ አስታወቁ።

39ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ በህብረቱ ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ ተካሂዷል።

የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ከጉባኤው ጎን ለጎን ከአፍሪካ ልማት ባንክ ፕሬዝዳንት ሲዲ ኡልድ ታህ(ዶ/ር) ጋር ተወያይተዋል።

የኮሚሽኑ ሊቀ መንበር ባንኩ ለአፍሪካ ቁልፍ የትኩረት መስኮች እያደረገ ያለውን ጠንካራ ድጋፍ ያደነቁ ሲሆን ለአፍሪካ ልማት ፈንድ 11 ቢሊን ዶላር ተጨማሪ ገንዘብ ድጋፍ ማድረጉን መልካም የሚባል እርምጃ መሆኑን አመልክተዋል።

ሊቀመንበሩ እና የባንኩ ፕሬዝዳንት ከእዳ፣ የአየር ንብረት ለውጥ እና የደህንነት ፈተናዎች ባለፈ የፋይናንስ አቅርቦት የአፍሪካ አበይት ፈተና መሆኑን በምክክራቸው ወቅት ገልጸዋል።

ሁለቱ ወገኖች የፕሮጀክት ዝግጅት ትብብርን ለማጠናከር፣ የአንድ ትሪሊን የአሜሪካን ዶላር የአፍሪካ ካፒታል ማሰባሰብ፣ የአፍሪካ የብድር ምዘና ኤጀንሲን ማጎልበትና ጠንካራ የአፍሪካ የፋይናንስ ስርዓት መገንባት ጉዳዮች ላይ መክረዋል።

በውይይቱ የአፍሪካ ህብረት እና የአፍሪካ ልማት ባንክ አጋርነታቸውን በአዲስ መልክ ለማደስ ተሠማመተዋለ።

በዓመት ሁለት ጊዜ ለመወያያት እና በአፍሪካ ፋይናንስ ላይ የከፍተኛ ደረጃ ምክክር ለማካሄድ እቅድ መያዛቸውንም ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል።